Wednesday, October 16, 2013

‹‹ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ መሞታቸው ተነግሮናል›› – (አቶ ስብሃት ነጋ)


ከዳዊት ሰለሞን
በኢትዮ – ኤርትራ ጦርነት ወቅት ያበሩት የነበረው የጦር አውሮፕላን ተከስክሶና ቆስለው በሻዕብያ እጅ ለሁለተኛ ጊዜ የወደቁት ጀግናው ኢትዮጵያዊ ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ በኤርትራ እስር ቤቶች በስቃይ ቆይተዋል፡፡
ጦርነቱ አብቅቶ ሁለቱ አገሮች የጦር ምርኮኞቻቸውን ሲቀያየሩ የኢትዮጵያ መንግስት በኮሎኔሉ ጉዳይ ገፍቶ መሄድ ባለመቻሉ በዛብህ ወደ አገራቸው ሳይመለሱ በኤርትራ እስር ቤት መቅረታቸውን የመንግስት ተቃዋሚዎች ይናገራሉ፡፡

የኮሎኔሉ ቤተሰቦች ደህንነታቸውን ይሰሙ የነበሩት ከአለም አቀፍ ቀይ መስቀል ሰራተኞች የነበረ ቢሆንም ግንኙነቱ መቋረጡን ለአብራሪው ቤተሰቦች ቅርበት ያላቸውና የኮሎኔሉ ወንድም ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ለላይፍ መጽሔት ሰጥተውት በነበረ ቃለ ምልልስ መናገራቸው ይታወሳል፡፡
የኮሎኔሉ ቤተሰቦች በተለያዮ ጊዜያት ወደ መንግስት አቤት በማለት አብራሪውን በዲፕሎማሲ ጥረት ከእስር እንዲያስፈቱ ሲወተውቱ ቢቆዮም መኖር አለመኖራቸውን እንኳን የሚያረጋግጥላቸው እስከማጣት መድረሳቸው ጉዳዮን ለፈጣሪ ከመስጠት የዘለለ አማራጭ እንዳይኖራቸው አድርጓል፡፡
የኢትዮጵያ የሰላምና ልማት ኢንስቲትዮትን የሚመሩት የቀድሞው የህወሃት ነባር ታጋይ አቶ ስብሃት ነጋ አሜሪካን አገር ጎራ ባሉበት አጋጣሚ ከገዛ ፓልቶክ ሩም ተሳታፊ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ‹‹ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ መሞታቸው ተነግሮናል፡፡አሁን እየጠየቅን የምንገኘው ከሞቱም ሬሳቸውን እንዲያሳዮንና የአሟሟታቸውን ምክንያት እንዲነግሩን ነው፡፡››በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡የፓልቶኩ አቅራቢም በኮሎኔሉ ሞት የተሰማትን ሀዘን በፓልቶኩ ስም ገልጻለች፡፡
የስብሃትን ንግግር ተከትሎ የኮሎኔሉ ቤተሰቦች በስብሃት የተነገረውን ከዚህ ቀደም መስማታቸውን ለማረጋገጥ ሞክረናል፡፡ የኮሎኔሉ ቤተሰቦች በዛብህ ሞተዋል ተብለው በይፋ አለመረዳታቸውን ባደረግነው የማጣራት ሙከራ ለማወቅ ችለናል፡፡ ስብሃት ነጋ በኤርትራ 27 የሚሆኑ ኢትዮጵያዊያን የጦር ምርኮኞች እንደሚገኙ በቃለ ምልልሳቸው አስታውቀዋል፡፡

No comments:

Post a Comment